TG Telegram Group Link
Channel: ማኅበረ ቅዱሳን ( Mahibere Kidusan)
Back to Bottom
ማኅበረ ቅዱሳን በተጨማሪ ማእከላት የደም ልገሳ መርሐ ግብር አከናወነ።


በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ሰንበት ትምህርት ቤቶች ማደራጃ መምሪያ ማኅበረ ቅዱሳን ከ ኢትዮጵያ የደም ባንክ ጋር በመተባበር ግንቦት 18 ቀን 2016 ዓ.ም የደም ልገሳ መርሐ ግብር በ25 ማእከላት ማከናወኑ ይታወሳል።

ይህ የደም  ልገሳ መርሐ ግብር ዛሬም በተለያዩ የማኅበሩ ማእከላት ላይ ቀጥሎ ውሏል።

ሰቆጣ፣ባሌሮቤ፣ዲላ እና ወሊሶ ማእከላት በዛሬው ዕለት የግቢ ጉባኤ ተማሪዎችን አባላትን እና ምእመናንን በማስተባበር የደም ልገሳ መርሐ ግብራትን አከናውነዋል።

ከመንፈሳዊ አገልግሎት በተጨማሪ በተለያዩ የማኅበራዊ ኃላፊነቶች ላይ ተሳትፎ እያደረገ የሚገኘው ማኅበረ ቅዱሳን ባከናወነው የደም ልገሳ መርሐ ግብር እጅግ በርካታ አባላት ተሳትፎ በማድረግ የብዙ ወገኖቻችንን ሕይወት መታደግ የሚችል ደም መለገስ ችለዋል።
የ፳፻ ፲ወ፮ ዓ.ም የርክበ ካህናት ቅዱስ ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኤ መግለጫ እንደሚከተለው ይነበባል።

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን፡፡

ከኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን
ቅዱስ ሲኖዶስ የተሰጠ መግለጫ፡፡

በመንፈስ ቅዱስ የሚመራው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስ በቅዱሳን አበው ሐዋርያት ትውፊት በፍትሕ መንፈሳዊ አንቀጽ 5 ቁጥር 164 በተደነገገው መሠረት ምልዓተ ጉባኤው የርክበ ካህናት መደበኛ ስብሰባውን ከግንቦት 21 እስከ ግንቦት 28 ቀን 2016 ዓ/ም ድረስ በርካታ አጀንዳዎችን በመቅረጽ ውይይት ሲያካሄድ ሰንብቷል፡፡

ምልዓተ ጉባኤው ለቤተ ክርስቲያናችን አንድነት፣ ለሐዋርያዊ ተልእኮ መስፋፋት፣ ለመንፈሳዊ ዕድገትና ለምእመናን ደኅንነት ትኩረት በመስጠት ለቅድስት ቤተ ክርስቲያናችንና ለሀገራችን ጠቃሚ የሆኑ ውሳኔዎችን አሳልፏል፡፡

በዚሁ መሠረት፡-

1.በቅድስት ቤተ ክርስቲያንና በሀገራችን መንግሥት መካከል ሊኖር ስለሚገባው መልካም የሥራ ግንኙነት በቅዱስ ፓትርያርኩ መሪነት ከመንግሥት የሥራ ኃላፊዎች ጋር የሚመካከር የብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት ልዑክ ቅዱስ ሲኖዶስ ሰይሟል፤

2.በመላው ሀገራችን በተፈጠሩ ግጭቶች፣ አለመግባባቶችና የሰላም ዕጦት በርካታ የሰው ሕይወት መጥፋትና የንብረት ውድመት እንደቀጠለ መሆኑ ቅዱስ ሲኖዶስን በእጅጉ አሳዝኗል፡፡ ስለዚህ ጉዳዩ የሚመለከታቸው ሁሉም ባለድርሻ አካላት ከግጭትና ከጥፋት ድርጊት ተቆጥበው የተፈጠረውን አለመግባባትና ግጭት በውይይትና በምክክር እንዲፈቱ እና ዘላቂ ሰላም እንዲረጋገጥ ቅዱስ ሲኖዶስ በአጽንኦት ጥሪውን ያቀርባል፤
3.በአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር እየተከናወነ ባለው የኮሪደር ልማት ምክንያት ለፈረሱ የቤተ ክርስቲያናችን ይዞታዎች የከተማ አስተዳደሩ ምትክ ቦታ በመስጠትና ቤተ ክርስቲያናችን ወደ መልሶ ማልማት እንድትገባ ድጋፍ በማድረግ፤ በተለይም ክብርት ከንቲባ ወ/ሮ አዳነች አበቤ በፈረሰው የጽርሐ ምኒልክ የቤተ ክርስቲያኒቱ ሕንፃ ምትክ በከተማ አስተዳደሩ ሙሉ ወጭ ተጨማሪ ምድር ቤትና የቦታ ስፋት ያለው B+G+4 ሕንፃ ገንብቶ ለማስረከብ ቃል በመግባትና የቤተ ክርስቲያናችን የበላይ ኃላፊ አባቶች በተገኙበት የመሠረት ድንጋይ እንዲጣል ማድርጋቸውን ቅዱስ ሲኖዶስ ከምስጋና ጋር የተቀበለው ሲሆን በተሰጠን ምትክ ቦታ ላይም የከተማው ፕላን በሚፈቅደው መሠረት የመልሶ ማልማት ሥራው እንዲከናወን ቅዱስ ሲኖዶስ ወስኗል፡፡

4.የሀገራዊ ምክክር ኮሚሽን ከተቋቋመበት አዋጅ መረዳት እንደሚቻለው ባለድርሻ አካላትን ባሳተፈ ሁኔታ ሀገራዊ ችግሮችን በምክክርና በውይይት ለመፍታት የተቋቋመ መሆኑን ተረድተናል፡፡ ይሁን እንጅ ሀገረ መንግሥትን ከመመሥረት ጀምሮ በአስታራቂነትና በሰላም ግንባታ ግንባር ቀደም ተጠቃሽ ለሆነችው እናት ቤተ ክርስቲያን እስከአሁን ድረስ በይፋ የቀረበ የተሳትፎ ጥሪ ሳይኖር ኮሚሽኑ የተሳታፊ ልየታንና አጀንዳ መረጣ አጠናቆ ወደ ምክክር ትግበራ እየገባ መሆኑ ቅዱስ ሲኖዶስን ቅር አሰኝቷል፡፡ በመሆኑም የቤተ ክርስቲያኒቱ ተሳትፎና አጀንዳ የማቅረብ መብቷ እንዲረጋገጥ ከኮሚሽኑ ጋር በመነጋገር ጉዳዩን ተከታትሎ ለፍጻሜ የሚያበቃ ኮሚቴ ቅዱስ ሲኖዶስ ሰይሟል፡፡

5.የብፁዓን አባቶች የዝውውርና የአህጉረ ስብከት ሥያሜን አስምልክቶ የቀረቡ ጥያቄዎችን ምልዐተ ጉበኤው ተመልክቶ ተገቢውን ውሳኔ አሳልፏል፤

6.የሃይማኖት ጉዳዮች ረቂቅ አዋጅ ላይ ቅዱስ ሲኖዶስ በሰፊው ከተወያየ በኋላ በረቂቅ አዋጁ ሊሻሻሉ ይገባቸዋል ብሎ ያመነባቸውን የማሻሻያ ሐሳቦች በማዘጋጀት ለሚመለከተው መንግሥታዊ ተቋም እንዲላክና ረቂቅ አዋጁ ከመጽደቁ በፊት የተሰጡት የማሻሻያ ሐሳቦች በረቂቁ ስለመካተታቸው ክትትል የሚያደርግ ኮሚቴ ቅዱስ ሲኖዶስ ሰይሟል፡፡

7.በቅዱሳት መጻሕፍት ላይ ተመሥርቶ አባታዊ ምክርና ተግሣጽ ማስተላለፍ ከቀድሞ ጀምሮ የነበረ መጽሐፍ ቅዱሳዊ መሠረት ያለው መሆኑ ቢታወቅም በሀገራችን ኢትዮጵያ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ በተፈጠሩ አለመግባባቶች የተከሰቱትን ወቅታዊ ችግሮች አስመልክቶ እየተላለፉ ያሉ ቤተ ክርስቲያንን የማይወክሉ መልእክቶችን ቅዱስ ሲኖዶስ የማይቀበላቸውና በጥብቅ የሚቃወማቸው መሆኑን እየገለጸ ወደፊት እንዲህ ዓይነት ተመሳሳይ ድርጊት እንዳይፈጸም ለማድረግ ይቻል ዘንድ ወጥ የሆነ የመግለጫ አሰጣጥና የትምህርተ ወንጌል ተልእኮ ሕገ ደንብ ተዘጋጅቶ ለምልዐተ ጉበኤ እንዲቀርብ ቅዱስ ሲኖዶስ ወስኗል፤

8.ግብረ ሰዶማዊነትና የተመሳሳይ ጾታ ጋብቻ በሕገ ተፈጥሮም ሆነ በሰው ልጅ የሰብዓዊ አኗኗር ፈጽሞ ተቀባይነት የሌለው፣ ፈጣሬ ዓለማት እግዚአብሔር መለኮታዊ ፈቃዱ በተገለጠባቸው ቅዱሳት መጻሕፍት ፈጽሞ የተከለከለ፣ በቀኖናተ ቤተ ክርስቲያን፣ በፍትሕ መንፈሳዊና በፍትሐ ብሔር ድንጋጌዎች፣ በሥነ ልቦና ደንቦች የተወገዘ፣ ሥነ አእምሮዊ ሚዛንን የሚያዛባ፣ ግለሰባዊ ማንነትን፣ ቤተሰባዊ ሕይወትን፣ ማኅበራዊ ትሥሥርን የሚጎዳ ተግባር በመሆኑ ቅዱስ ሲኖዶስ እያወገዘ የተመሳሳይ ጾታ ጋብቻና የግብረ ሰዶማዊነትን ኃጢአት በተመለከተ የቅድስት ቤተ ክርስቲያንን አቋም በሚገልጽ መልኩ ራሱን ችሎ ዓለም አቀፋዊ ይዘቱን ባገናዘበ ሁኔታ ዝርዝር መግለጫ እንዲሰጥ ቅዱስ ሲኖዶስ ወስኗል፤

9.በደቡብ የሀገራችን ክፍል የቤተ ክርስቲያኒቱን አብነት ትምህርት ከማስፋፋትና ከፍ ያለ መዐርግ ከመስጠት አንፃር የጋሞና አካባቢው ዞኖች ሀገረ ስብከት የዝጊቲ ደብረ ሰላም አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ ቤተ ክርስቲያን የአራቱ ጉባኤያት ማስመስከሪያ ትምህርት ቤት እንዲሆን በቀረበው ጥናት መሠረት ቅዱስ ሲኖዶስ ለምሥክር ጉባኤ ቤቱ ዕውቅና በመስጠት ወደ ትግበራ እንዲገባ ወስኗል፡፡

10.ከሀገራችን ውጭ ባሉ አህጉረ ሰብከት መደበኛ አገልግሎት ለመስጠት የሚላኩ አገልጋዮች በክፍሉ ሊቀጳጳስ ሲጠየቅ በሙያ ብቃታቸው፣ በምግባራቸውና በመንፈሳዊነታቸው የተመሰከረላቸው አገልጋዮች ከሁሉም አህጉረ ስብከት በብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት አቅራቢነት በውድድር እየተለዩ በቋሚ ሲኖዶስ ውሳኔ እንዲላኩ ቅዱስ ሲኖዶስ ወስኗል፡፡

11.የቅድስት ቤተ ክርስቲያን አስተዳደር ዘመኑን የዋጀ እንዲሆን ቅዱስ ሲኖዶስ የዐሥር ዓመት መሪ ዕቅድ በማጽደቅ ወደ ትግበራ እንዲገባ መወሰኑ ይታወሳል፡፡ በዚሁም መሠረት ለአፈጻጸሙ ያመች ዘንድ በባለሙያዎች ተዘጋጅቶ የቀረበውን መዋቅራዊ አደረጃጀት በማጽደቅ በሕገ ቤተ ክርስቲያኑና በቃለ ዓዋዲው ተካቶ ሥራ ላይ እንዲውል ቅዱስ ሲኖዶስ ወስኗል፡፡

12.በመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቤተ ክህነት ጽ/ቤት ተዘጋጅቶ የቀረበውን የ2017 ዓ.ም. ዓመታዊ በጀት በማጽደቅ በሥራ ላይ እንዲውል ቅዱስ ሲኖዶስ ወስኗል፡፡

በአጠቃላይ ቅዱስ ሲኖዶስ በመንፈስ ቅዱስ እየተመራ ላለፉት ተከታታይ ቀናት በመንፈሳዊ፣ ማኅበራዊና ሀገራዊ ጉዳዮች ላይ በመወያየትና ተገቢውን ውሳኔ በማስተላለፍ መደበኛ ስብሰባውን በዛሬው ዕለት በጸሎት አጠናቅቋል፡፡ መሐሪና ሁሉን ቻይ የሆነ እግዚአብሔር አምላካችን ለሀገራችን፣ ለሕዝባችን፣ ለዓለሙ ሁሉ ሰላሙን፣ ፍቅሩንና አንድነቱን ይስጥልን፡፡
እግዚአብሔር ኢትዮጵያንና ሕዝቦቿን ይባርክ
ወስብሐት ለእግዚአብሔር አሜን

አባ ማትያስ ቀዳማዊ
ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአክሱም
ወዕጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት

ግንቦት ፳፱ ቀን ፳፻፲፮ ዓ.ም. ኢትዮጵያ አዲስ አበባ
ቅዱስ አባ አበስኪሮን

ዳግመኛም በዚህች ቀን ቀሊን ከምትባል አገር ቅዱስና ቡሩክ ድል አድራጊም የሆነው አባ አበስኪሮን በሰማዕትነት ሞተ።

➯ይህም ቅዱስ ከእንዴናው ገዥ ከአርያኖስ ጭፍራ ውስጥ ነበር የከሀዲው ንጉሥ የዲዮቅልጥያኖስ ስለ አምልኮ ጣዖት የሆነች ትእዛዙ በደረሰች ጊዜ። ወዲያውኑ ይህ ቅዱስ በሕዝብ መካከል ተነሥቶ ንጉሡን ረገመው ጣዖታቱንም ሰደበ ወታደር ስለ ሆነም ያሠቃየው ዘንድ ማንም አልደፈረም ነገር ግን በንጉሥ አዳራሽ ውስጥ አሠሩት።

➯መኰንኑም ወደ ሀገረ አስዩጥ በሔደ ጊዜ ወደ ንጉሥ ላከው ከእርሱም ጋራ ሌሎች ወልፍዮስ፣ አርማንዮስ፣ አርኪያስ፣ ጴጥሮስ፣ ቀራንዮስ የተባሉ ነበሩ እሊህም ክብር ይግባውና ስለ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ደማቸውን ሊአፈሱ ከአባ አበስኪሮን ጋራ ተስማሙ።

➯በንጉሡም ፊት በቆሙ ጊዜ በጌታችን ታመኑ ንጉሡም ትጥቃቸውን ይቆርጡ ዘንድ በየአይነቱ በሆነ ሥቃይም እንዲአሠቃዩአቸው አዘዘ ንጉሡ እንዳዘዘም አደረጉባቸው። ከእኒህ ከአምስቱ ግን ራሶቻቸውን የቆረጡአቸው አሉ የሰቀሉአቸውም አሉ እንዲህም ገድላቸውን ፈጽመው የሕይወት አክሊልን ተቀበሉ።

➯የከበረ አበስኪሮስን ግን ታላቅ ግርፋትን እንዲገርፉት አዘዘ ከዚያም በኋላ ከራሱ እስከ አንገቱ ቆዳውን እንዲገፉ በፈረስ ጅራትም አሥረው በከተማው ውስጥ እንዲጐትቱት አዘዘ ይህንም ሁሉ አደረጉበት።

➯ከዚህም በኋላ በብረት ምጣድ ውስጥ አድርገው በላዩ አፉን ዘግተው ተሸክመው ወስደው በውሽባ ቤት ማንደጃ ውስጥ ጨመሩት በሥቃዩም ውስጥ ሁሉ የእግዚአብሔር መልአክ ወደርሱ ይመጣና ያጽናናው ነበር ያስታግሠውም ነበር ያለ ምንም ጉዳት አድኖ በደኅና ያስነሣው ነበር።

➯ከማሠቃየቱም በደከመ ጊዜ ከሥራየኞች ሁሉ የሚበልጥ በሥራዩም ወደ አየር ወጥቶ ከአጋንንት ጋራ የሚነጋገር ሥራየኛ አመጣለት። እርሱም የውሽባ ቤቱን ዘግተው ሽንት እንዲረጩበት አዘዘ እንዲሁም አደረጉ። እባብንም ይዞ በላዩ አሾከሾከና ለሁለት ክፍልም ሁኖ ተሠነጠቀ መርዙንና ሆድ ዕቃውን ወስዶ በብረት ወጭት አድርጎ አበሰላቸው በውሽባ ቤቱ ውስጥ ወደ አባ አበስኪሮን አቅርቦ ያንን መርዝ ይበላ ዘንድ ሰጠው ቅዱሱም በላ ግን ምንም ምን ጉዳት አልደረሰበትም።

➯ያም መሠርይ የመኳንንተ ጽልመት አለቃቸው ሆይ በዚህ ክርስቲያናዊ ላይ ኃይልህን አድርግ ብሎ ጮኸ ምንም ምን ጥፋት ባልደረሰበት ጊዜ መሠርዩ አደነቀ።

➯ቅዱስ አበስኪሮንም መሠርዩን የሚራዳህ ሰይጣንህስ በክብር ባለቤት በጌታዬ በኢየሱስ ክርስቶስ ኃያል አንተን ይቀጣሃል አለው። ወዲያውኑ ጥሎ የሚያንከባልለው ክፉ ሰይጣን ተጫነበት ክብር ይግባውና በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ እስከ ታመነ ድረስ አሠቃየው። መኰንኑም የመሠርዩን ራስ ይቆርጡ ዘንድ አዘዘና በሰማዕትነት ሞተ።

➯በቅዱስ አበስኪሮን ላይ ግን ቁጣና ብስጭትን በመጨመር ጽኑዕ ሥቃይን አሠቃየው አባለ ዘሩንም እንዲቆርጡ አዘዘ እርሱ ግን በመከራው ሁሉ እግዚአብሔርን ያመሰግን ነበር። ከዚህም በኋላ ራሱን በሰይፍ እንዲቆርጡ አዘዘና ቆረጡት የድል አክሊልንም በመንግሥተ ሰማያት ተቀበለ።

➯ከቅዱስ አበስኪሮን ተአምራትም አንዱን አንነግራችኋለን በግብጽ ደቡብ በስሙ የታነፀች ቤተ ክርስቲያን ነበረች ካህናቷም ከፉ ሥራ የሚሠሩ ክፉዎች ነበሩ ቅዱስ አበስኪሮንም ከክፋታቸው ተመልሰው ንስሓ ቢገቡ ብሎ ጠበቃቸው። ባልተመለሱ ጊዜ ግን የንዳድ በሽታ አምጥቶ ሁሉም በአንዲት ጊዜ ሞቱ።

➯ከዚህም በኋላ ቅዱስ አበስኪሮን ተቀምጦ የላዕላይ ግብጽ የሆነች ብያሁ ወደምትባል አገር ደረሰ የአገር ሰዎችም በደጃቸው ተቀምጠው ሳይተኙ በጨረቃ ብርሃን እርስ በርሳቸው ያወሩ ነበር። የከበረ አበስኪሮንም ከፊታቸው ደርሶ ሰላም ለእናንተ ይሁን አላቸው በአዩትም ጊዜ የሰላምታውን አጸፋ እየመለሱ ተነሥተው ተቀበሉት ሁለተኛም ያቺን የሚሻትን ምድር እያመለከታቸው ከምድራችሁ ጥቂት እንድትሰጡኝ እሻለሁ አላቸው እነርሱም ጌታችን እንደወደድክ ይሁንልህ አሉት መቶ የወርቅ ዲናርም ሰጥቷቸው ተሠወራችው።

➯እነርሱም ከዚህ ራእይ የተነሣ አደነቁ። ከተኙ በኋላም ቤተ ክርስቲያኒቱን አፍልሶ ከግብጽ ደቡብ ወደ ላዕላይ ግብጽ ብያሁ ወደምትባል አገር በመቶ የወርቅ ዲናር ወደ ገዛት ምድር ከንዋየ ቅድሳቷ ሁሉና ከዐፀዷ ጋር አምጥቶ በዚያ አቆማት።

➯የሀገር ሰዎች በጠዋት ነቅተው ወደ ውጪ በወጡ ጊዜ ቤተክርስቲያኒቱን በደጃቸው አገኙዋት እጅግ ፈጽሞም አደነቁ ምስጉን እግዚአብሔርንም አመሰገኑት። ከዚያች ጊዜ ጀምሮ ድንቅ ተአምር የሚደረግባት ሆነ።


➯ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በቅዱሳኑ ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋራ ትኑር ለዘላለሙ አሜን።

#ስንክሳር ሰኔ 7
HTML Embed Code:
2024/06/14 08:01:36
Back to Top