TG Telegram Group Link
Channel: Nolawi ኖላዊ
Back to Bottom
የሕይወት ሥነ ሥርዓት 10

…. አለባበስህን ጠብቅ (ካለፈው የቀጠለ)

አንዳንድ ሰዎች ስለ ራሳቸው በአፋቸው ብዙ ያወራሉ ፤ ሌሎች ደግሞ በልብሳቸው ስለራሳቸው ብዙ ያወራሉ ። ልብስ ዕርቃን መሸፈኛ ነው ። ዕራቁታችንን የሚያውቀንና የሚቀበለን እግዚአብሔር ብቻ ነው ። ሰው ያለ መሸፈኛ የማይቆም ፍጡር ነው። በሰው ፊት ለመቆም ልብስ ፣ በእግዚአብሔር ፊት ለመቆም ጸጋ ያስፈልገዋል ። ልብስ ከመሠረታዊ ፍላጎቶች አንዱ ነው ። ልብስ ሰዎች ጤናቸውን የሚጠብቁበትም ነው ። የአእምሮ በሥራ ላይ መሆን አንዱ ምልክት ልብስ መልበስ ነው ። በርግጥ እንደ ምዕራባውያን መራቆትም ፣ እንደ ዐረብ ሴቶች መጨቆንም ሁለቱም ሚዛናዊ መሆን አለበት ። ልብስ ሀብትን ማሳያ ፣ ቁንጅናን ማጉያ አድርገው የሚጠቀሙበት አሉ ። የሰው ልጅ ለራሱና ለሰዎች ብሎ የሚያደርገው ነገር ካለ እርሱ ልብስ ይበላል። ልብስ ሙሉ ሰውን ፣ ሹምን ፣ ካህንን ለመለየት የሚውል ነው ። ልብስ ትልቅ የክብር መግለጫ ነው ። የሰው ልጆችም እንደ ዕፀ በለስ በልብስ የሚፈተኑ ሆነዋል ። ላለበሰና ለለበሰ ሰው እኩል ክብር የላቸውም ። ኖር ለልብሱ ይባላል ። ኖር ለእርሱ ሳይሆን ኖር ለልብሱ መባሉ ተገቢ አይደለም።

የዓለማችን ትልቁ ምርት ከምግብ ቀጥሎ ልብስ ነው ፤ ከዚያ ቀጥሎ መድኃኒት ሊሆን ይችላል ። ጸሎታችንም “የዕለት ጉርሴን ፣ የዓመት ልብሴን አትንሣኝ” የሚል ነው ። ልብስ የሚያገለግለው ዕራቁትን ለመሸፈን ብቻ ስይሆን የሰውነት ቅርጽንም ለመሸፈን ነው ። የሰውነትን ቅርጽን ማሳየት በራሱ እንደ መራቆት ነው ። ልብስ የሰው ልጆችን ውበት የሚያላብሳቸው ነው ። ዕራቁቱን የሚያምር ከሕፃን በቀር ማግኘት አስቸጋሪ ነው ። ልብስ ከቅድስና መለኪያዎች አንዱ ነው ። ብዙ ጊዜ ልቅ አለባበስን በሚመለከት ከወንዶች ይልቅ ሴቶች ይፈተናሉ ። “የሴት ክብር ባሏ ሲገልጣት እንጂ በአደባባይ ተገልጣ ስትለምን አይደለም” ይባላል ። ሰዎች ሁሉ በዓለም ላይ ያሉ ወገኖች ልብስን በተለያየ ዓላማ ሊለብሱ ይችላሉ ።

የመጀመሪያው ፋሽን ለመከተል ነው ። የፋሽኑ ዓለም እንቅልፍ የለውም ። የሰዎችን ቀልብ ለመሳብና ገንዘብ ለመልቀም ሌሊትና ቀን ይተጋል ። የፋሽኑ ዓለም ከአጋንንት ጋር የእውቀት ልውውጥ እንደሚያደርግ ብዙ ሲነገር ኖሯል ። ሰዎችን ምን ይማርካቸዋል ? በማለት ያጠናሉ ፣ ያስጠናሉ ። በይበልጥ ዝሙትን የሚያስፋፋ ፣ ሥጋዊ ስሜትን አድራሻ ያደረገ ንድፍ ይሠራል ። ሰይጣን አያመነዝርም ፣ ግን ዝሙትን ይወዳል ። ክፉ ነገሥታትም ትውልድ የዝሙት እስረኛ ከሆነ እነርሱን ስለማያያቸው በዚህ ጦር ወግተው ያቆስሉታል ። ፋሽኑ ከተሰፋ ልብስ እስከ ተቀደደ ልብስ ፣ ከፍዝ እስከ ቦጌ ቀለም እየለዋወጠ ያመጣል ። የሰውን ወረተኛነት ትልቅ የገቢ ምንጭ በማድረግ ጠባዩን ይዋጉታል ። ዓለምን የሚመሩ ጥቂት ሰዎች ናቸው ። ዕውቅ ሰዎች ያንን ልብስ ለብሰው ሲታዩ ጎጋው ሕዝብ ይከተላል ። የልብሱ ትርጉም ምን መሆኑን እንኳ ሳይጠይቅ የለበሰውን እየጣለ ያንን ይሸምታል ። የፋሽኑ ዓለም የጊዜ ክፍተት እየሰጠ የሄደውን ፋሽን መልሶ እያመጣ አዲሱን ትውልድ ይጫወትበታል ። ፋሽን ተከታይ የሆኑ ዘመናዊና ንቁ ሰዎች እንደሆኑ ይገምታሉ ፣ ሰዎችም እንደ ዘመናዊ ያስቧቸዋል። ለልብሱ የሚጨነቅ ለነፍሱ የማይጨነቅ ደንቆሮ ነው ። እውነተኛ ሥልጣኔ ግን ከልብስ ያለፈ ነው ።

ሁለተኛው ማራኪ ለመሆን ነው ። ሴቶች ወንዶችን ለመሳብ ፣ ወንዶች ሴቶችን ለመሳብ ይለብሳሉ። በእጃቸው ላይ የሚቀቡት ሽቶ ሳይቀር የሚጨብጡት ሰው እጅ ላይ ታትሞ እንዲቀር ፣ አካባቢው ሁሉ በእነርሱ ጠረን እንዲታወድ ይፈልጋሉ ፤ ይህ መለስተኛ ጣዖትነት ነው ። ለዚህ ነው “ሽቶ የዝሙት ቅብዐ መንግሥት ነው” የሚባለው ። ከወደድነው ሁሉ ጋር አንኖርም ፣ የወደደን ሁሉም ከእኛ ጋር አይኖርም ። ከልብሳችን ይልቅ ጠባያችን ሳቢ ቢሆን የሰው ዋጋ እናገኛለን ። አሊያ የሸቀጥ ማስታወቂያ ሆነን እንቀራለን ። በዕድሜአቸው ዘመን ምንም የሚነገር ታሪክ የሌላቸው ፣ ልብስ ሲገዙ ፣ ሽቶ ሲያጠራቅሙ ኖረው ሞቱ የሚባሉ ብዙ ምስኪን ሰዎች አሉ።

ይቀጥላል

ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
ሚያዝያ 1 ቀን 2016 ዓ.ም.
የማርቆስ  ወንጌል ትርጓሜ 14

ማር.2:18-28

በ#ዲያቆን #አሸናፊ #መኮንን የተዘጋጀ ስብከት
Audio
የማርቆስ ወንጌል ትርጓሜ 14

ማር. 2፣ 18- 28

ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
የሕይወት ሥነ ሥርዓት 11

…. አለባበስህን ጠብቅ (ሐ)


ልብስን በሚመለከት ሰዎች የተለያየ አመለካከት ይኖራቸዋል ብለን ሁለቱን አይተናል ። ሰዎች ልብስን የሚለብሱት ሦስተኛው ብዙዎች ስለለበሱት ሊሆን ይችላል ። የብዙኃን ድምፅ ያሸንፋልና ለምን? ሳይባል የሚለበሱ ልብሶች አሉ ። የተጣበቀ ጠባብ ልብስ ሁሉ ሰው ስለለበሰው እኛ መልበስ ላያስፈልገን ይችላል ። የፋሽኑ ኢንዱስትሪ ትልቁንም ትንሹንም ወጣት ማስመስል የሚፈልግ ነው ። ሽምግልናም የራሱ ውበት አለው ። የራሱ አለባበስም አለው ። ይልቁንም በዕድሜ ከፍ ያሉ ወጣትነትን አይተውታልና ወጣት ለመምሰል ባይሞክሩ የተሻለ ነው ። ወጣቶች ሽምግልናን አላዩትምና ቢናፍቁት ወግ ነው ።

አራተኛ፡- ብዙዎች ስለማይለብሱት ሊሆን ይችላል ። አንዳንድ ሰዎች ብዙዎች የለበሱትን ይጠሉታል ። ከፋብሪካው በራሳቸው ስም የታተመ ልብስ ያሠራሉ ። ከጀማው ጋር መጋፋት ድሀ መሆን ይመስላቸዋል ። በእውነት ልብስ የሀብት ማሳያ መሆኑ ዕድሜ ለቻይና ጊዜው ያለፈ ሆኗል።

አምስተኛ፡- ለማጭበርበር ሊሆን ይችላል ። ሙሉ ልብስ ለብሰው ፣ ፕሮቶኮላቸውን ጠብቀው ፣ እንግሊዝኛ እያወሩ ፣ ትልልቅ ሀብትን እየተነተኑ የሚዘርፉ ብዙዎች ናቸው ። ለእነዚህ ሰዎች ልጃቸውን መዳር የሚፈልጉ ብዙ ሴት ወይዘሮዎች አሉ ። እነዚህን ማግባት የሚፈልጉ ብዙ ሀብታም ሴቶች ሊኖሩ ይችላሉ ። “እህ ትበል እናትሽ ልብሴን አይታ የዳረችሽ” የሚባለው ታሪክ የደረሰባቸው ሴቶች ብዙ ናቸው ። ውድ መኪኖችን ተከራይተው የሚያጭበረብሩ አያሌ ናቸው ። የትልልቅ ተቋማት መኪኖችን በመያዝ ባለሥልጣን ነኝ እያሉ ሞኞችን ገደል የሚከትቱ የተካኑ ሌቦችን ይህች ከተማ ይዛለች ። ቤቶቹና ፎቆቹ አፍ ቢኖራቸው ብዙ ይናገሩ ነበር ።

ስድስተኛ፡- ከማኅበረሰቡ ላለመለየት መናኛ የሚለብሱ አሉ ። አንዳንድ ሀብትና ሥልጣን ያላቸው ሰዎች “ልብስ ስመርጥ ጊዜ አላጠፋም” ብለው የወደዱትን አንድ ቀለም ያለውን ልብስ ስድስት ይገዛሉ ። ዓመት ሙሉ አንድ ዓይነት ኮት ስለሚለብሱ ልብስ የማይቀይሩ ይመስለናል ። ዛሬ በአንዳንድ ከተሞች የሚታገቱ ሰዎች ለየት ያለ ልብስ የለበሱ ናቸው ። “በሮም ሲኖሩ እንደ ሮማውያን” የሚባለው ለዚህ ነው ። ዓለም ከጉልበት ይልቅ ለጥበብ እጅ ትሰጣለች ። ስንኖር ጠቢብ መሆን መልካም ነው ። የቆዩት ሀብታሞች ብዙ የሚለብሱ አልነበሩም ። በዚህ ምክንያት አንድ ዓይነት ጨርቅ ስለሚለብሱ “ልብሳቸው ላይ አስደግመው ነው” የሚላቸው ብዙ ነበር ።

ሰባተኛ፡- የሥራ ጠባያቸው ስለሚያስገድዳቸው የሚለብሱ አሉ ። የባንክ ፣ የሆቴል ፣ የተለያዩ ተቋማት ሠራተኞች ሙሉ ልብስ እንዲለብሱ ይገደዳሉ ። ባንኮች አንድ ተራ አለባበስ የለበሰ ሠራተኛ ቢያስቀምጡ ኖሮ ማንም አምኖ ገንዘብ አያስቀምጥም ነበር ። ትምህርት ቤቶች የተማሪዎችን አንድ ዓይነት ልብስ መደንገጋቸው ያስመሰግናል ። በቤተ ክርስቲያንም ሁሉም ነጭና ርካሽ ነጠላ ለብሶ ማስቀደሱ ትልቅ ጥበብ ነው ። በሌሎች አብያተ ክርስቲያናት የልብስና የጫማ ውድድር አድክሞአቸዋል ። አስተማሪያቸውም የሚያወራው ልብሱን ከየት አገር እንዳስመጣው ነው ። ድሀ እዚህ መሐል ምን ይሠራል !

ስንለብስ በአቅማቸው አነስ ያሉ ሰዎች ያሉበት ከሆነ እንዳናሳቅቃቸው መጠንቀቅ ያስፈልጋል ። ያላቸውን አጥበውና ለብሰው በመጡበት ስፍራ ደግሞ ዝቅ ያለ አለባበስ ብንለብስ ይሸማቀቃሉ። ስንለብስ አካባቢውንና ሁኔታውን ማገናዘብ አለብን ። የኀዘንና የሰርግ ልብስ መለየት አለብን። ልቅሶ ቤት ነጭ ለብሰን ብንሄድ “የደስ ደስ መጣ” ብለው ይዘምቱብናል ። ጥቁር መልክ ካለን ነጭ መልበስና ቀይ ከሆንን ጥቁርን ብንለብስ የተሻለ ነው ። ልብሳችን ብዙ ዓይነት ቀለም መከተል የለበትም ። ቢያንስ ከሁለት ቀለም ማለፍ የለብንም ። ጫማችን የልብሳችንን አንደኛውን ቀለም ቢከተል መልካም ነው ። የቀለም ምርጫችን በራሱ የውስጣችንን ማንነት ይገልጣል ።

ልብሳችንን ማጠብና መተኮስ ግድ ነው ። ድሀ የሆነው ወታደር ይህንን የሚያደርግ ከሆነ ሌላው ጎበዝ መሆን አለበት ። ስለ ቆሸሸን ሰው ይሸሸናል እንጂ አያዝንልንም ፣ መንፈሳዊ አድርጎም አይመለከተንም ። በትዳር ላይም አንዱ ወገን ንጽሕናውን የማይጠብቅ ከሆነ መራራቅን ይወልዳል ። እስከ ፍቺም እንደሚደርስ ከልምዳችን መናገር እንችላለን ። ትዳር መግባት ገደል መግባት አይደለምና ራስን መጣል ተገቢ አይደለም ። ራሳችሁን ስትጥሉ እንኳን ሌላው ሊወዳችሁ ራሳችሁንም መቀበል ያቅታችኋል ። ውኃን ርካሽ አድርጎ የሰጠን ጌታ ለንጽሕና ብሎ ነው ። የሥራ ልብስ ፣ የስፖርት ልብስ መለየት አለብን ። ልብሳችንን በመልክ በመልኩ ማስቀመጥ በቀላሉ አይቶ ለመልበስ ይረዳናል ። ብዙ ጨርቅ ማብዛትም በሽታ ነው ። ከሁሉ በላይ እኛ ለምናየው ለውስጥ ልብሶቻችን ዋጋ መስጠት አለብን ። አደራ ሙሉ ልብስ ለብሰን ፣ የተቀደደ ካልሲ ማድረግ ራስን መናቅ ነው ። ያየ ሰውም ይንቀናል ። “ውስጡን ለቄስ “ ብሎ ይተርትብናል ። ለውስጥ ልብሶቻችን ንጽሕና ትልቅ ዋጋ መስጠት አለብን ።

ሰማይን በከዋክብት ፣ ምድርን በአበባ ያስጌጠ እግዚአብሔር እኛም በሥርዓት እንድንለብስ ይፈልጋል ! አልባሽ እርሱ ነውና “የዕለት ጉርሴን ፣ የዓመት ልብሴን ስጠን” እንለዋለን ።

ይቀጥላል

ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
ሚያዝያ 5 ቀን 2016 ዓ.ም.
የዘመናችን ፈተና 8
  መለኪያ መጥፋት

በ#ዲያቆን #አሸናፊ #መኮንን የተዘጋጀ ስብከት

አሁን በቴሌግራም ቻናል ይለቀቃል ። ይከታተሉ

የዲያቆን አሸናፊ መኰንን ትምህርቶችና ስብከቶች ለመከታተል ከሥር የተቀመጡትን ገጾች ይመልከቱ፡-

https://hottg.com/Nolawii

https://hottg.com/nolawisebketoch

https://www.facebook.co m/ashenafi.mekonnen.357

https://youtu.be/3qfQp9yYmHY

www.ashenafimekonen.com
Audio
የዘመናችን ፈተና 8
. መለኪያ መጥፋት
መስፈርት የሌለበት ዘመን

(የወጣት አገልጋይ ፈተና)

ወዳጁን ለማግኘት የሚጓዝ እግር በደመና ላይ እንደሚንሳፈፍ ያህል ይሰማዋል ። ሩቅ መንገድ በፍቅር ምክንያት ቅርብ ነው ። ተራራውን ሜዳ ፣ ሸለቆውን ሙሉ የማድረግ አቅም ወትሮም የፍቅር ነው ። ብዙ ዓይነት ፍቅር ባለበት ዓለም ላይ ብዙ ዓይነት ወዳጆችም አሉ ። ወላጆች ፣ አብሮ አደጎች ፣ የሙያ አጋሮች ፣ የትዳር ጓዶች ፣ ልጆች … ወዳጆች ተብለው ይጠራሉ ። የመምህርና የተማሪ ፍቅር ግን ከዚህ ሁሉ ይለያል ፤ ይበልጣልም ። የፍቅሩ መሠረት በሥጋ መወለድ ሳይሆን ከእግዚአብሔር መወለድ ነው ። ግቡም ምድራዊ ርስት ማውረስ ሳይሆን ሰማይ ማድረስ ነው ። ሩቅ መንገድ የሚጓዝ ፍቅር መንፈሳዊ ብቻ ነው ። ምድራዊው ፍቅር ከፊት ወረት ፣ ከኋላ ሞት ይገድበዋል ። ቅዱስ ጳውሎስ በጸሎት ምጥ ፣ በአገልግሎት ጭንቅ የወለደኝ መንፈሳዊ አባት ነው ። እኔ ለኤፌሶን ምእመናን አባት ብሆንም የእኔ አባት ግን እርሱ ነው ። እርሱን ለማግኘት ያውም በመጨረሻው የዕድሜ ዘመኑ ጥሪውን ተቀብዬ ስመጣ ትልቅ ደስታ ይሰማኛል ። በአንድ ዓይኔ አለቅሳለሁ ፣ መሄጃው ጊዜ ደርሷልና ። ምድር መካሪዋን ስታጣ ትጨነቃለች ። በሁለተኛው ዓይኔ እስቃለሁ ። መምህሬን ላገኝ ነውና ።

ተማሪ መምህሩን በጣም ከመውደዱ የተነሣ የአባቱን ስም በመምህሩ ይቀይራል ። ያማረ ምግብ ሲያገኝ ወጣትነቱና የመብላት ፍላጎቱ ሳያሸንፈው “ይህን ለመምህሬ” ይላል ። የመምህሩን እግር እያጠበ ዘወትር ይመረቃል ። መምህሩንም ሲጠራ “የኔታ” ይላል ፣ የኔ ጌታ ማለት ነው ። ፍቅሩ ታላቅ አክብሮት ያለበት ነው ። ተመርቆ የወጣ እንደሆነ በዓመት አንድና ሁለት ጊዜ የቀድሞ ተማሪዎችን አስተባብሮ ፣ ካገኘው ላይ በረከት ይዞ መምህሩን ይጠይቃል ። መምህሩም ምድራዊ ወገንና ዘመዶቹን ክዶ ተማሪዎቹን ዘመድ አድርጓልና ደስ ይለዋል ። ወጉ ይህ ነው ፤ የመምህርና የተማሪ ወግ የሌለው ዘመን ዘመነ አዳፋ ነው ። ከአባቴ በፊት ነበርሁ የሚል ልጅ በትዕቢት አእምሮውን ያጣ ነው ። በሥጋ መውለድ ልዩ ችሎታ አይደለም ፣ በእውቀት መውለድ ግን ልዩ ተሰጥኦና ትልቅ አባትነትም ነው ። ልደት ያላገኙ አእምሮዎች የገዳይነት ዋሻ ናቸው ። መምህሩ የነፍስ አባት ነውና ነፍስን በእውቀት ይወልዳል ። ሰው ገንዘብ ቢሰጠን ከኪሱ ነው ፣ እውቀት ግን የነፍስ ስጦታ ነውና ከሁሉ ይበልጣል ። መምህራን ክብር ይገባቸዋል ። እንኳን የሰማይን መንገድ ይቅርና “የሮም መንገድ በዚህ በኩል ነው” ያለ ሰው ውለታው አይረሳም ። መምህሩ ሲዋረድ ተማሪ እያነሰ ይመጣል ። ተማሪ ሲጠፋ ትውልድ የጨለማ እስረኛ ይሆናል ። ተማሪ መምህሩን ሲያዋርድ ሰይጣን ታናሽ ወንድም ይሆናል ። መንፈሳውያን መምህራን ክብራቸው ሊመለስ ይገባል። ቀዳሽ ቢቀድስ ፣ ሰባኪ ቢሰብክ ፣ ማኅሌታይ ቢዘምር ምንጩ መምህራን ናቸው ። “ማን ላይ ቆመሽ ፣ ማንን ታሚያለሽ?” እንዲሉ ።

በጉዞዬ ቅዱስ ጳውሎስ ስለ አገልጋዮች መስፈርት የነገረኝን እያስታወስሁ ነበር ። አገልግሎት መስፈርት የለውም ። አገልጋዮች ግን መስፈርት አላቸው ። መስፈሪያው የእግዚአብሔር ቃል ነው ። በምድራዊ መስፈሪያ ተለክተው ሲታጩ የሚፈጥሩት መደናገር ብዙ ነው ። ቤተ መንግሥቱንና ቤተ ክህነቱን ለማገናኘት ባለ ሁለት መታወቂያ ናቸው ተብለው ሲታጩ የማያቋርጥ ማዕበል በቤተ ክርስቲያን ላይ ያመጣሉ ። አዝማደ መንግሥት ናቸው ተብለው ሲሾሙ ከእግዚአብሔር ይልቅ ጎሣቸውን ያገለግላሉ ። በሰው ታምነው ደረጃውን የወጡ የታመኑበት ሲታመም ፣ እነርሱም ትኩሳት ይጀምራቸዋል ። በወኔና በማስፈራራት ስፍራ ሲሰጣቸው ደጋጎችን ስፍራ ይነሣሉ ። በጉቦና በመማለጃ አባት ልሁን ሲሉ አባትነት ስጦታ እንጂ ግዥ አይደለምና ለብዙዎች መጥፋት ምክንያት ይሆናሉ ። “ነውር ካለባቸው ይታዘዛሉ” ተብለው በማሸማቀቂያ ካርድ ሲሾሙ “ከዚህ በኋላ ማን ይነቀንቀኛል ? ለራሱ ሲል ሁሉም ይጠብቀኛል” ብለው ክፋታቸውን ሕጋዊ ያደርጉታል ። መስፈርት የሌለው ግለሰብ የቆሻሻ መጣያ ነው ። መስፈርት የሌለው አገር ሲመክን የሚኖር ነው ። መስፈርት የሌላት ቤተ ክርስቲያን እንደ ድመት ወልዳ የምትበላ ናት ። መስፈርት ያስፈልጋል ። በእውነት መስፈርት ቢኖር የተገፋው ባለወንበሩ ፣ የተነቀፈው ባለ ሙያው መሆኑ ይታወቅ ነበር ። ቤተ ክርስቲያን ዘመድ ማፍሪያ ፣ የወንዝ ለወንዝ ጨዋታ መናኸሪያ ስትሆን ከነገድ ከቋንቋ የዋጃት ክርስቶስ ያዝናል ። መጥቀምና መጠቃቀም ለቤተ ክርስቲያን የጉዳት ዘመንን ያመጣባታል ። በቤተ ክርስቲያን ለተቸገሩት እርዳታ እንጂ ሥልጣን አይሰጥም ። ላልተማረና መንፈሳዊነት ለሌለው ሥልጣን መስጠት ለእብድ ሰይፍ መስጠት ነው ።

ይህን እያሰብሁ ከሮም ሕንፃዎች ጋር አወራ ነበር ። አዎ መስፈርት ያስፈልጋል ። መስፈርቶቹም ወደ አእምሮዬ ይመጣሉ ። መስፈርት ሲጠፋ ወጣቱ አገልጋይ መስፈርት በሌላቸው ሰዎች እየታወከ ይመጣል ።

ጢሞቴዎስ ነኝ ክፍል 13

ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
ሚያዝያ 7 ቀን 2016 ዓ.ም.
የሕይወት ሥነ ሥርዓት (12)

9- ሰላምታ ስጥ

ሰላምታ የግንኙነት የመጀመሪያው ምዕራፍ ነው ። ሰላምታ የወዳጅነት ፣ የናፍቆት ፣ የስብሰባ ፣ የስብከት ፣ የደብዳቤ ፣ የአዋጅ ፣ የቃለ ምዕዳን መክፈቻ ነው ። ሰላምታ የተቋማት መግለጫ ነው። ካህን ፣ ወታደር ፣ እስካውት ፣ ስፖርተኛ ፣ ሙስሊም ፣ ክርስቲያን በሰላምታ ይለያል ። ሰላምታ እንስሳት እንኳ ሲገናኙ በቋንቋቸው የሚገልጡት የፍቅር ንባብ ነው ። ሰዎች እንስሳትን ፣ እንስሳት ሰዎችን በሰላምታ ይቀበላሉ ። ሰላምታ ለሚያውቁት ሰው ብቻ ሳይሆን ለማያውቁት ሰውም የሚሰጥ ስጦታ ነው ። ሰላምታ በሃይማኖት ዓለም አምልኮ ነው ። በሰላምታ የሚመሰገነው እግዚአብሔር ነውና ። ሰላምታ በሰላም የመምጣታችን ማስገንዘቢያ ነው ። ሰላምታ ካልሰጠን ሰዎች በክፉ እንደመጣን ገምተው በክፉ ይዘጋጃሉ ። ሰላምታ የሰውን ልብ የምናስከፍትበት የመጀመሪያው የደወል ድምፅ ነው ። አንድ ሙሉ ሰው ሰላምታ ማቅረብ የሚችል ሰው መሆን አለበት ። ልጆችን ገና በጠዋቱ ሰላምታ መስጠትን ማለማመድ አለብን ። “ሰላምታ ስጡ” ስለሚባል ሰላምታ ስጦታ ነው። ሁሉም ሰው መስጠት የሚችለው ስጦታ ነው ።

የአንዳንድ ሰዎች ሰላምታ በጣም ይማርካል ። “ምነው ሰላም ባሉኝ!” በማለት ሰው ሁሉ ይጓጓል ። ሰላምታ ሰውነትና መንፈሳዊነት ባላቸው ትውልዶች የተከበረ ዕንቈ ነው ። ገንዘብን እንጂ ፍቅርን ለማይፈልግ ሆድ አደር ትውልድ ግን ሰላምታ ጊዜ ማጥፊያ ነው ። በአገራችን እስከ ቅርብ ዓመታት በመንገድ የተገናኘ ሰው ሰላምታ ይለዋወጣል ። ከየት እንደ መጣ ፣ ወዴት እንደሚሄድ አውርቶ የአቅሙን ያህል ድጋፍ ያደርጋል ። አሁንም በገጠሩ ሰውና ሰው ሲገናኝ ሰላምታ ይሰጣጣል ። “ከብት እንኳ ሲገናኝ እምቧ ይባባል ።” ሰው ሰውን ሲያገኝ ሰላም ሊል ይገባዋል ። በየመንገዱ ቆም ብለን የምንለዋወጠው ሰላምታ የራሳችንን ዋጋ የሚጨምር ፣ ደስታን የሚያጎናጽፍ ነው። ደግሞም መነጋገር ትልቁ የአእምሮ ጭንቀት ማስተንፈሻ ነው ። ከንግግር ውስጥ ብልሃት ይገኛል ። በአገራችን አንዱ የአንዱ የሥነ ልቡናው አካሚ ሆኖ ኖሯል ። ብዙ ችግር ቢኖርም ጭንቀት እንዳይኖር ብዙ ማስተንፈሻዎች ነበሩ ። ልቅሶውን ፣ ኀዘኑን ፣ ጭንቀቱን የምናስተናግድበት የዜማ መንገዶች ፣ የግጥም ድርድሮች አሉን ። በመድኃኒት ከሚገኝ ፈውስ በእርስ በርስ ፍቅር የሚገኝ ፈውስ ትልቅ ዋጋ ያለው ነው ።

የሰላምታ ባለጠጋ መሆን አለብህ ። ጌታ በትእዛዝ ቃሉ፡- “ሰላምታ ስጡ” ብሏል ። (ማቴ. 10 ፡ 13 ።) ወደ ቤት ስትገባ ፣ ወደ ሥራህ ስትሰማራ ፣ ስብሰባ ስትከፍት ሰላምታ መስጠት አለብህ ። ሰላምታህ ለቀጣይ ጉዳይ በር ከፋች ነው ። በሩ ካልተከፈተ ማለፍ እንደማይቻል ሰላምታህ ውጤታማ ካልሆነ ምንም መስጠትና መቀበል አትችልም ። ሰላምታህን ከሚጎዱ ነገሮች ውስጥ ጥቂቱን እንይ ። ጨፍጋጋና ኮስታራ ፣ ቍጠኛ ፊት ሰላምታን ይጎዳል ። ፈገግ ማለት የራስህንም ቆዳ ማፍታታት ነው ። ደግሞም እውነተኛ ፈገግታ ከፀሐይ ብርሃን ይልቅ ያምራል ። ኑሮ የጨለመባቸው ባንተ እውነተኛ ፈገግታ ሊበራላቸው ይችላል ። “ለካ ዛሬም ፈገግታና ሳቅ አለ” እንዲሉ ያደርጋቸዋል ። ስለ ተኮሳተርህ አትከበርም ፣ ፈገግ ስላልህ አትናቅም ። የክብር መገኛው ወይ ፍቅር ወይ ፍርሃት ነው ። ፍርሃት የሚያመጣው ክብር ሰዎችን እንዲሸሹህ ያደርጋል ። የፍቅር አክብሮት ግን እንደ ማለዳ ፀሐይ ብርሃኑን እየጨመረ እንደሚሄድ ነው ።

ሰላምታህን የሚጎዳው ኩራት ያለበት ድምፀትህ ነው ። ከመሬት ተነሥቶ ልጥጥ የሚል ሰው አትሁን ። ቃላትህንም እያስረዘምህና እየበጣጠስህ ከአፍህ አታውጣ ። ወንበር ሠርተህ ካልነገሥሁ አትበል ። ትዕቢት ራስን በቅጡ ያለማወቅ ውጤት ነው ። ደግሞም የባዶነት ማሳያ ነው ። ዓለት ጉብ ብሎ ፣ ከብዶ የሚኖር ነው ። ሲፈረከስና ራሱን ሲያሳንስ ግን ቤት መሥሪያ ፣ መንገድ ማውጫ የሚሆን ነው ። ጠቃሚ የምትሆነው በትሕትና ብቻ ነው ። የገዛ ክንፏ የከበዳት ወፍ መብረር አትችልም ። ትዕቢትም ራስን ማክበድ ፣ የራስን ሬሳ መሸከም ነው ። ። ሰላምታን የሚጎዳው ሌላው የምትመርጣቸው ቃላት ናቸው ። ሰዓቶችን ለይ ። ማታ ላይ እንዴት አደራችሁ? አይባልም ። ሰላምታ ስትሰጥ ከቀልብህ መሆን አለብህ ። ደግሞም የሰዎችን መዐረግ ማወቅና በመዐረጋቸው መሠረት መጥራት አለብህ ። ሰላምታህ በሚያግባባችሁ ነገሮች ብቻ የታጀበ መሆን አለበት ። ገና ከበር ጠብ የሚጀምር ባለጌ ነው ። ቅሬታ ሰላምታህን ይጎዳዋልና አስቀድመህ መፍታት አለብህ ።

ሰላምታ አልችልም አይባልም ። በሕይወት ውስጥ ትንሹና ቀላሉ ነገር እርሱ ነውና ። ምናልባት ተፋትተው ይሆናልና በሰላምታህ ዳር ዳሩን በል እንጂ ወደ ትዳሩ አትግባ ። ምናልባት ሞቶበት ይሆናልና “እገሌስ?” ብለህ ስትጠይቅ ጠንቃቃ ሁን ። ምናልባት ከፍቶት ይሆናልና በቀልድ አትጀምር ። ሰላምታህ ግን ያንን ሰው ነጻነት የሚሰጠው መሆን አለበት ። ይልቁንም ወደ ቤትህ የመጣው ሰው ለመቆየትም ላለመቆየትም የሚወስነው በሰላምታህ መጠን ነው ። አንተ በዚህ ምድር ላይ ቤት የለህምና በቤትህ እንግዳ የሆንከው አንተ ሆይ ! እንግዳ ተቀበል ።

ሰላምታህ አባት የሆነ እንደሁ ጉልበትና እጁን መሳም ያስፈልግሃል ። ፓትርያርክ እንደሆነ ብፁዕ አባታችን አይባልም ። ቅዱስ አባታችን ወይም ብፁዕ ወቅዱስ እያልህ ሰላምታህን አቅርብ ። ጳጳስ የሆነ እንደሁ ብፁዕ አባታችን ብለህ ጥራ ። የሲኖዶስ አባላት ፊት ስትቆም ቅዱስ አባታችን፣ ብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት ብለህ በየመዐርጉ ሰላምታ አቅርብ ። መሳይና ወዳጅህን ስታገኝ እንደ ቅርበትህ በእጅህ ጨብጥ ። እንደ ቅርበትህ መሳሳምን አትርሳ ። ይሁዳ ጌታን ስሞታል ። በእውነት ቢሆን መልካም ነበረ ። በእውነት መሳም የፍቅር መግለጫ ነው ። ሕፃናት ከሆኑም የምታውቀውን ሕፃን ስትስም የማታውቃቸውንም ሕፃናት አብረህ ሳም ። ስታዋራቸውም በርከክ ብለህ ፊት ለፊት እያየህ አዋራቸው ። አንድ ቀን አድገው “ያን ጊዜ ሕፃን ሳለን ታከብረን ነበር” ብለው ሊያመሰግኑህ ይመጣሉ ። የሰው ሚስትና እጮኛን በጣም ሰላም ማለትና መቀራረብን ተዉ ። ባልዋ በሌለበትም የሰው ቤት አትሂድ ። ወደ ባል ስትደውል “ሚስትህን ሰላም በልልኝ” በል ። ማንንም ሰው ስታገኝ አንገትህን ዘንበል አድርገህ ሰላም በል ። ሰው ልዑል ፣ የንጉሥ ልጅ ነውና ። ማክበር መከበር ነው ። ክብርህን ግዛው እንጂ አትሽጠው ። ባለጌንም ከወዳጅህ ጋር አታስተዋውቅ ። ምንም ቢከፋህ የልብህን ችግር በፊትህ አደባባይ ላይ አታስነብብ ። እዚህ ላይ ላቆም እንዳላደክምህ !

ሰላም ይብዛልህ !

ይቀጥላል

ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
ሚያዝያ 9 ቀን 2016 ዓ.ም.
ተመስገን ጌታዬ

ጸጋህ አይጓደል ተመስገን ጌታዬ ፣
ሁሉን ያረክልኝ ባለውለታዬ ፤
አንድ አለኝ የምልህ ዘወትር ሁልጊዜ ፣
አንተ ነህ ጋሻዬ ደጋፊ ምርኵዜ ።
አቤቱ አምላክ ሆይ የሰማይ አባቴ ፣
አካሌ ሲደክም አንተ ነህ ጉልበቴ ፤
በሰላም በጤና ስኖር በዕድሜ ጸጋ ፣
ምስጋና ብቻ ነው የምሰጥህ ዋጋ ።

የኑሮዬ ባላ የሕይወቴ ቤዛ ፣
ለእኔ ያረክልኝ ውለታህ የበዛ ፤
ተመስገን ፈጣሪ ልበልህ ጠዋት ማታ ፣
ረዳቴ አንተ ነህ የቸገረኝ ለታ ።
ሲርበኝ አጉርሰህ ስታረዝ አልብሰህ ፣
ስጨነቅ አጽናንተህ ስታመም ፈውሰህ ፣
ድረስልኝ ስልህ ስምህን ጠርቼ ፣
የምፈልገውን አላውቅም አጥቼ ።

ቸኩለህ እንደ ሰው ቅጣት የማትሰጠው ፣
ሀብታምና ድሀ የማታስበልጠው ፤
ቸሩ መድኃኔ ዓለም ይድረስህ ምስጋና ፣
ረዳቴ አንተ ነህ በስምህ ልጽናና ።
ለኮንትራት ሕይወት ነገ ለሚቀረው ፣
በመንፈስ አጽናኝ ቃልህን እንዳልሽረው ፤
ኃጢአቴን ሰርዘህ አድነኝ ከዕዳ ፣
መሐሪው አንተ ነህ ለሰው ልጆች ፍዳ ።

እመካብሃለሁ በሰማዩ አባቴ ፣
የፈጠርከኝ አምላክ አውጣኝ ከኃጢአቴ ፤
ሳዝን ፈጥነህ ደራሽ ስከፋ መካሪ ፣
መከታ ጋሻዬ አንተ ነህ ፈጣሪ ፤
ዕዝራ በመሰንቆ ዳዊት በበገና ፣
እንዳቀረቡልህ ለሥራህ ምስጋና ፣
አወድስሃለሁ እኔም በዜማዬ ፣
አንተ ነህ ጠባቂ የሕይወት ጋሻዬ ።

(ምንጭ፡- ዘለሰኛ)

ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
ሚያዝያ 10 ቀን 2016 ዓ.ም.
የማርቆስ ወንጌል ትርጓሜ 15

ማር. 3: 1-6

ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
የሕይወት ሥነ ሥርዓት (13)

10- ሥራህን ተግተህ ሥራ

ሥራ እግዚአብሔር ለሰው ልጆች ከሰጠው ጸጋ አንዱ ነው ። ሥራ ርግማን ሳይሆን በረከት ነው ። አዳም ሲፈጠር ገነትን እንዲያበጃትና እንዲንከባከባትም ነው (ዘፍ. 2 ፡ 15) ። ደግሞም ምድርን ግዛ ተብሎ ሥልጣን ሲሰጠው ትልቅ ሥራ እንደ ተሰጠው ያሳያል ። ምድር ለእርሱ ስጦታው ናትና እንደ ራሱ ገንዘብ አድርጎ መንከባከብ ይገባዋል ። ከበደል በኋላ ግን “በፊትህ ወዝ እንጀራን ትበላለህ” ተባለ (ዘፍ. 3 ፡ 19) ። ይህ ሥራ ርግማን መሆኑን የሚያሳይ ሳይሆን ከበደል በኋላ አዳም ብዙ ልፋት ጥቂት ትርፍ ይገጥመዋል ማለት ነው ። በዚህም ምክንያት እርካታ እያጣ እንደሚመጣ የሚገልጥ ነው ። እያንዳንዱ ሰው ለሚኖርበት ዓለም የሚያደርገው አስተዋጽኦ አለው ። ሰው የሁለት ዓለም ፍጡር ነውና ለምድር ኑሮው መሥራት ፣ ለሰማዩ ኑሮ ማመን አለበት ። ሥራ በረከት ነው ።

በአእምሮ ላይ የሚነሣውን የሰይጣንን ፈተና ለማሸነፍ ሥራና ጸሎት ሁለቱ መሣሪያ መሆናቸውን አባቶች ተናግረዋል ። ሥራ የፈታ አእምሮ ለሰይጣን መናገሻ ከተማ ነው ። ነገረኛ ሰዎች ሥራ የማይሠሩ ወይም አጉል ትርፍ የሚያገኙ ወገኖች ናቸው ። በሥራ የተጠመደ ነገርን ይሸሻል ። ንጹሕ አእምሮ ለማግኘት ሥራ መሥራት መልካም ነው ። ተነፋፍቆ ለመገናኘት ሥራ አስፈላጊ ነው ። የሰው ልጆች ያለማቋረጥ ከተያዩ ግንኙነቱ ይደፈርሳል ። በዓለም ላይ በተነሣው የቅርቡ ወረርሽኝ ሰው ሁሉ እቤቱ እስረኛ ሁኖ ነበር ። ብዙ ትዳር ፈርሷል ። ብዙ ግንኙነት ተበላሽቷል ። ወንጀሎች ተፈጽመዋል ። ሰዎች ለአእምሮ ጭንቀት ተዳርገዋል ። እስካሁን ድረስም ጠባሳው እያወከ ይገኛል ። ሥራ በረከት ነው ። አሁንም በቤታቸው ተቀምጠው የሚሠሩ ሰዎችን በተለያየ ዓለም እንሰማለን ። የሰይጣን ትልቁ ውጊያው ሰውና ሰው እንዳይገናኝ ማድረግ ነው ። ሥራ ያገናኛል ። ሥራ ከቤታችን ውጭ ሲሆን ለብሰን እንወጣለን ። ለራሳችን እንክብካቤ እናደርጋለን ። ከሰዎች ጋር በማውራት ብቻ ነጻ አእምሮ እናገኛለን ። አአምሮአችን ትልቅ ኃይል የተሸከመ ነውና ማረፊያ ያገኛል ። ማረፊያ ያላገኘ አእምሮ ዓለምን ለማጥፋት አቅም አለው ።

ሥራው አለቃ የሆነለት ሰው ውጤታማ ነው ። ሥራ ብዙ እንቅልፍን የሚጠላ በመሆኑ ሠራተኛ ሰው ማልዶ መነሣት አለበት ። ሥራ አካላዊ ፣ ሥነ ልቡናዊና መንፈሳዊ በረከትን ይሰጣል ። አካላችን የሚጠነክረው በሥራ ነው ። የምድር ተግዳሮትን የሚቋቋሙ ሰዎች ሠራተኛ ሰዎች ናቸው ። የዓለም መንግሥታት ትልቅ ስኬታቸውን የሚለኩት የሥራ ዕድልን በመፍጠራቸው ነው ። በአጭር ቋንቋ እግዚአብሔር ሰነፍ ልጅ የለውምና ሥራን መውደድ ይገባናል ። የሐዋርያው ቃልም ቁርጥ ያለ ነው፡- “ሊሠራ የማይወድ አይብላ ።” (2ተሰ. 3 ፡ 10) ። ስብሰባ ፣ ኮሚቴ ፣ ቃለ ጉባዔ የሚሉ ሰዎች አብዛኛዎቹ ሥራ የማይወዱ ፣ ቁጭ ብለው መነዛነዝ የሚያፈቅሩ ናቸው ። ሕይወትን ቀለል አድርጎ መኖር የሚቻለው በስብሰባ ሳይሆን በሥራ ነው ። ጨካኝ መንግሥታት ሕዝባቸውን በስብሰባ ያደነዝዛሉ ። መሪ የሆኑት ደግሞ ሕዝባቸውን ለሥራ ያነሣሣሉ ። ሕዝብን በሥራ መወጠር ከሁከትም ይጋርዳል ።

አዎ ሥራህን በታማኝነት ሥራ ። ጸልየህ ያገኘኸውን ሥራ በትጋት አለመሥራት እግዚአብሔርን ማሳዘን ነው ። ሥራ ታማኝነትና ትጋት ይፈልጋል ። ታማኝነቱ ትጋት ከሌለው ፣ ትጋቱ ታማኝነት ከሌለው አደገኛ ነው ። ሥራህ የሃይማኖትህ ቦታ አይደለም ። በሥራህ ቦታ ሥነ ምግባርን እንጂ አምልኮን ልፈጽም አትበል ። ጉቦን ተጸየፍ ። ደመወዝህ እንዲባረክ ጸልይ ። ጉቦ ያለህንም ይዞት የሚሄድ ፣ ልጆችህንም የሚያሳብድ ነው ። ጉበኞች የብዙዎችን እንባና ደም ተሸክመው ይሄዳሉ ። ሰው ወዶና ፈቅዶ እንጂ ተጨንቆ የሚሰጠን ነገር ርግማን የሚያመጣ ነው ። የሥራ ሰዓትህን አክብር ። ደመወዝህ አነስተኛ በመሆኑ ባለጉዳዩን ማንገላታት አይገባህም ። ባለጉዳይህን ፣ ያንተን ሙያ የሚፈልገውን እግዚአብሔርን እንደምታገለግል አድርገህ አገልግለው ። የሙያህ ባለቤት እግዚአብሔር ነው ። በሙያህ ሰውን አታጉላላ ። አንድ ቀን ይህ አእምሮህ ላይሠራ ይችላል ። እጆችህ ላይሠሩ ይችላሉ ። በሚያልፈው አካልህ የማያልፍ ሥራ ሥራበት ። በሙያ ሰውን ማስደሰት መታደል ነው ። ካንተ የሆነ ምንም ነገር የለም ።

ሥራ የምትሠራው አሥራትህንም ለማውጣት ነው ። ባንተ የሥራ ትርፍ የእግዚአብሔር ቤት ይገነባል ። ብዙዎች ወንጌል ይሰማሉ ። ልጆችህ ጠግበው ያድራሉ ። ትዳርህ አይታወክም ። የብዙ ትዳር ሁከትም የገቢ ማነስ ነው ። ሥራ ትልቅና ትንሽ የለውም ። በምድር ላይ የሚያሳፍረው ቆሻሻ መጥረግ ሳይሆን ቆሻሻ ጠባይ መያዝ ነው ። ጌታችን ለእኛ አርአያ ለመሆን አናጢነትን ሠርቷል ። ቅዱሳን ሁሉ ሥራቸውን በትጋት ሲሠሩ ለሰማያዊ ግዳጅ የተጠሩ ናቸው ። ትጉ ሠራተኛ ትጉህ ሐዋርያ ሊሆን ይጠራል ። ትጋት ተወዳጅ ያደርጋል ። ለክብር ለመታጨት ያበቃል ።

እግዚአብሔር የእጅህን ሥራ ይባርክ !

ይቀጥላል

ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
ሚያዝያ 12 ቀን 2016 ዓ.ም.
የዘመናችን ፈተና 9
  መለኪያ መጥፋት

በ#ዲያቆን #አሸናፊ #መኮንን የተዘጋጀ ስብከት

አሁን በቴሌግራም ቻናል ይለቀቃል ። ይከታተሉ

የዲያቆን አሸናፊ መኰንን ትምህርቶችና ስብከቶች ለመከታተል ከሥር የተቀመጡትን ገጾች ይመልከቱ፡-

https://hottg.com/Nolawii

https://hottg.com/nolawisebketoch

https://www.facebook.co m/ashenafi.mekonnen.357

https://youtu.be/3qfQp9yYmHY

www.ashenafimekonen.com
Audio
የዘመናችን ፈተና 9
መለኪያ መጥፋት
ከአገልግሎት በፊት

ሰው ብቻውን አይሆንም ። ወይ ከእግዚአብሔር አሊያም ከራሱ ጋር ያወጋል ። ሰው ካገኘም ከሰው ጋር ያወራል ። ትዝታም እንደ አሁን ትኩስና ወቅታዊ ሁኖ ያነጋግረዋል ። የመምህር ቃልም ከሚኖረው ኑሮ ጋር ሲገጣጠም እንደ ገና አዲስ ፍንዳታ ሁኖ በውስጡ ይጮኻል ። መስፈርት እጅግ አስፈላጊ መሆኑን ቅዱስ ጳውሎስ የነገረኝን ከኤፌሶን ቤተ ክርስቲያን አስተዳደር ጋር ማነጻጸር የጀመርኩት አሁን ነው ። ቤተ ክርስቲያን በእምነት የምትቀበል ፣ በፈሪሀ እግዚአብሔር መስፈርት የምትሾም ናት ። የአገልግሎት የመጀመሪያው መስፈርት ፍላጎት ነው ። አገልግሎት ጊዜን ሳይሆን ሕይወትን ሰጥተው የሚገቡበት ነው ። አገልግሎት የፍትፍት ሰደቃ ሳይሆን የመስቀል ጉዞ ነው ። ገሀነምን ከሚያህል የእሳት ዓለም ነፍስ ሲያወጡ ወላፈኑ አይንካኝ ማለት ሞኝነት ነው ። የአገልግሎት ጉዞ ራስን መካድ ያለበት ነው ። ራሴን ከዛሬ ጀምሮ ያለ ክርስቶስ አላውቀውም ብሎ መማል ይጠይቃል ። ይልቁንም ኦርቶዶክሳዊው/ቀጥተኛው ጎዳና ብዙ እንግልት ከውስጥና ከውጭ ያለበት ነው ። ከክርስቶስ ጋር ያልሞተ ፣ ገና ውዳሴና ክብርን ነቅዐ ሐሰት ከሆነው ከሰው ልጅ የሚናፍቅ ጉዞው ይከብደዋል ። ኦርቶዶክሳዊው አገልግሎት በመከራ እድናለሁ ሳይሆን በመከራ የድኅነት ጉዞዬን እፈጽማለሁ ብሎ የሚያምን ነው ።

ኦርቶዶክሳዊው አገልግሎት የሀብት ውድድር ያለበት አይደለም ። ኦርቶዶክሳዊው አምልኮ ስሜትን የሚያነቃቃ ሙዚቃና ጭፈራ ሳይሆን ተመሥጦ ያለበት ነው ። ኦርቶዶክሳዊው ክርስትና ስማዕትነት ያለበት ነው ፣ የጥብዐት/ቅዱስ ጭካኔ/ መንገድ ነው ። ራሱን ያልካደ ፣ የብልጽግና ወንጌል ሰባኪ ፣ የስስት ጦር የወጋው ፣ ግለኝነትን አምላኪ ፣ የራሱን ደሴት መሥርቶ ልጄ ሚስቴ እያለ ኗሪ ኦርቶዶክሳዊው መንገድ አይመቸውም ። ሃይማኖት ከሰው ያልተቀበልነው ፣ በሰው የማንጥለው ነው ።

አገልግሎት ሥራ ቢሆንም በሙያ ብቻ ሳይሆን በጸጋው የምንወጣው ሰማያዊ ግዳጅ ነው ። ወታደርበራሱ ትጥቅ እንደማይዋጋ አገልጋይም የመንፈስ ቅዱስ የጦር ዕቃ በሆነው በጸጋ ያገለግላል ። ቢሆንም የአገልግሎት መስፈርቱ ፍላጎት ነው ። አገልጋይ የሚሆነው በርግጥ መቍረጡ ፣ ዓለምን መካዱ መፈተን አለበት ። ይህን የመሰለ ቆንጆ አንድ ደብር ይገባዋል ብሎ አገልግሎትን ማርከስ ቀጥሎ ያረክስናል ። ጳጳሱ መፍራት ያለበት ዲቁና ሲናቅ ነው ። ዲቁና ሲናቅ ቅስና ይናቃል ፤ ቅስና ሲናቅ ጵጵስና ይናቃል ። አገልግሎት መስፈርት ከሌለ ሰላማዊ ሰልፍ ያማረው ሁሉ ወደ ዐውደ ምሕረቱ ይጠጋል ። ቄሣርን ለመዋጋት ቤተ ክርስቲያንን ምሽግ ያደርጋታል ። ቤተ ክርስቶስ ዘእግዚአብሔር መባሏ ቀርቶ ቤተ ክርስቲያን ዘጴጥሮስ ፣ ቤተ ክርስቲያን ዘጢሞቴዎስ ትባላለች ።

ራሱን የመራ ቤቱን ይመራል ። ቤቱን የመራ አገርና ቤተ ክርስቲያንን ይመራል ። አገልጋይ በግል ሕይወቱና በቤቱ መመዘን አለበት ። ንብረት ጠባቂ እንኳ ሥነ ምግባሩ ይታያል ፣ ተያዥም ይጠራል ። ነፍስን የሚጠብቀው አገልጋይማ ኑሮው መገምገም አለበት ። አገልጋይ በንግግሩ ፣ በአመጋገቡ ፣ በመጠጡ ፣ በግንኙነቱ ፣ በአስተያየቱ ልከኛ መሆን አለበት ። በሁለት ክንፍ በቤተ ክርስቲያንና በዓለም ካልበረርኩ ማለት የለበትም ። ቁጥብነት መከራን ባያስቀርም ይቀንሳል ። እጅግ መራራ ከሆኑ መተፋት አለ ፤ እጅግ ጣፋጭ ከሆኑም ማለቅ አለ ። ድንበር የሌለው አገልጋይ ሁሉ ይደፍረዋል ። ሁሉን ላስደስት የሚልም ሁሉ ይከፋበታል ። ሰውን ብናስደስት እግዚአብሔር ሊያዝንብን ይችላል ። እግዚአብሔርን ስናስደስት ግን እግዚአብሔርን የሚያውቅ ይደሰትብናል ።

ራስን መግዛት የአገልግሎት ትልቅ መስፈርት ነው ። በከተማ ላይ የበላይ ከመሆን በራስ ላይ የበላይ መሆን የተሻለ ነው ። ራስን አለመግዛት ለጸጸት ይዳርጋል ። በሕይወት ሰልፍ ውስጥ ታጋሽ ያልሆነ ሰው ራስን ባለመግዛት ይፈተናል ። ራስን መግዛት በሁሉም ነገሮች ውስጥ ያስፈልጋል ። በፍቅር ራሱን ያልገዛ ከመውደድ አልፎ አምልኮ ውስጥ ይገባል ። የወደደውን ሰው ሲያጣ ሞቱን ይመኛል ። በቸርነት ራስን መግዛት ይገባል ። ችግር በተወራበት ፣ መዋጮ በሚጠየቅበት ቦታ ሁሉ በስሜት እሰጣለሁ የሚሉ ሲጨነቁ እናያለን ። በቁጠባም ራስ መግዛት ይገባል ። ለጤናቸው እንኳ ገንዘብ ላለማውጣት የሚሰስቱ ሰዎች አሉ ። የሰበሰብነውን አንድ ቀን የማናውቀው ሰው ይበላዋል ። በቅጡ መጠቀም መልካም ነው ። በእውነት እያንዳንዱ ተልእኮ አገልግሎት ነው ። ሠራተኛ ሁሉ አገልጋይ ነው ። ስለዚህ ራስን መግዛት ይገባቸዋል ። አዳራሹ በስብሰባ ሲግል ራስን ባለ መግዛት ሹሞችን የሚሳደቡ ሲወጡ ይጨነቃሉ ። ያጨበጨበላቸው ሕዝብም የት ደረሱ አይላቸውም ። በርግጥ ነገሥታት የመከራቸውንም ሰደበን እንደሚሉ የታወቀ ነው። ቢሆንም ስንገሥጽም ራስን በመግዛት ሊሆን ይገባዋል ።

አዎ አገልግሎት የተገነባ ሰብእናና ፣ ያጌጠ መንፈሳዊነት መስፈርቱ ነው ።

ጢሞቴዎስ ነኝ ክፍል 14

ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
ሚያዝያ 14 ቀን 2016 ዓ.ም.
የሕይወት ሥነ ሥርዓት (14)

11- ቀጠሮ አክብር

እግዚአብሔር አምላክ ቀጠሮን በማክበር የታወቀ አምላክ ነው ። የ5550 ዘመንን ቀጠሮ ያከበረ ብቸኛ አምላክ ነው ። ሐዋርያው ይህን ሲገልጥ እንዲህ ብሏል፦ “ነገር ግን የዘመኑ ፍጻሜ በደረሰ ጊዜ እግዚአብሔር ከሴት የተወለደውን ከሕግም በታች የተወለደውን ልጁን ላከ፤” (ገላ. 4 ፡ 4) ።
እግዚአብሔር በቀጠሮው ማርፈድ ወይም መዘግየት አያውቅም ። ይህንንም ነቢዩ እንዲህ ሲል ገልጧል፡- “ራእዩ ገና እስከ ተወሰነው ጊዜ ነው፥ ወደ ፍጻሜውም ይቸኵላል፥ እርሱም አይዋሽም ቢዘገይም በእርግጥ ይመጣልና ታገሠው እርሱ አይዘገይም ።” (ዕን. 2 ፡ 3) ።

ይህች ዓለም በእግዚአብሔር ቀጠሮ ተይዛ ያለች ዓለም ናት ። 5500 ዘመን የድኅነት ቀጠሮ ነበራት ። ላለፉት ሁለት ሺህ ዓመታት የሚመጣውን ንጉሥ እየጠበቀች ነው ። የዚህች ዓለም ትልቁ እንግዳ የመጣውና የሚመጣው ኢየሱስ ክርስቶስ ነው ። እርሱ ከእኛ ሳይለይ እመጣለሁ ያለ ፣ መንበሩን ሳይተው በበረት የተወለደ ነው ። በኖኅ ዘመን የጥፋት ውኃ መቼ እንደሚመጣ ፣ መቼ እንደሚቆም ተናግሮ ፣ የተናገረውንም የፈጸመ አምላክ ነው።

አምልኮተ እግዚአብሔር ታላቅ ቀጠሮ ነው ። ከእግዚአብሔር ጋር ከመገናኘት የበለጠ ቀጠሮ የለምና ። በብሉይ ኪዳን በመገናኛው ድንኳን የጠዋትና የማታ መሥዋዕት በጊዜው ይቀርባል ። የሳምንትና የዓመት አገልግሎትም ከቀጠሮ ሰዓቱ ዝንፍ አይልም ። በዓላት የሰውና የእግዚአብሔር ቀጠሮ ናቸው ። ወላጅ ለበዓል ልጆቹን እንደሚጠበቅ እግዚአብሔርም በሰንበትና በበዓላት ልጆቹን ይጠብቃል ። በዓላት የቤተሰብ ፍቅርን እንደሚጠብቁ ፣ መንፈሳዊ በዓላትም ሃይማኖትን በሰዎች ልብ ትኩስ ያደርጋሉ ። የተደመሰሱ አብያተ ክርስቲያናት አንዱ ችግራቸው በዓላት የሌላቸው መሆኑ ነው ። ደግሞም በዓላት የአንድ ሕዝብ የነጻነት ምልክት ናቸው ።

ተፈጥሮ እግዚአብሔር የሰጠውን ቀጠሮ ያከብራል ። ተፈጥሮ በራሱ ቸር አይደለም ። አንዳንድ ሰዎች የተፈጥሮ ችሮታ እያሉ ያወራሉ ። በተፈጥሮ በኩል የቸርነት እጁን የሚገልጥ እግዚአብሔር ብቻ ነው ። ተፈጥሮ ራሱን የሚመራ ሳይሆን ፈጥሮ የሚያስተዳድር አምላክ አለ ። ይህ ሁሉ አስደናቂ ተፈጥሮ የታላቅ ፍንዳታ ውጤት አይደለም ። ታላቅ ፍንዳታ ይህን ውበት ከሰጠ ፣ ትንንሽ ፍንዳታ ያለባቸው የኢራቅና የጋዛ ከተሞች ውብ በሆኑ ነበር ። ተፈጥሮ ለእግዚአብሔር ቀጠሮ የተገዛ ነው ። ሌሊትና ቀኑ ክረምትና በጋው በሰዓቱ ይመጣሉ ። የመስቀል ወፍ ፣ አደይ አበባ በሰዓቱ ሲመጡ ሰው እንዴት ቀጠሮ የሚስት ይሆናል ?

ቀጠሮን አክብር ። ይበልጥ ለአምልኮተ እግዚአብሔር ወደ ቤተ ክርስቲያን የምትሄድበትን ቀጠሮ አክብር ። ምነው ከአምልኮተ እግዚአብሔር ውጭ ወደ ቤተ ክርስቲያን ይኬዳል ወይ ? አዎ ጓደኛ ለማግኘት ፣ የወደዳት ልጅ ሰላም ማደሯን ለማረጋገጥ የሚሄዱ አሉ ። ለረብሻ ፣ ለፖለቲካ የሚሄዱ አሉ ። የዘር ዕድር ለመጠጣት ፣ የስለላ ተግባራቸውን ለማከናወን የሚሄዱ አሉ ። እግዚአብሔር ቤት ለመሄድ የምናረፍደው የሚመለከተንና የማይመለከተን አምልኮ ያለ ስለሚመስለን ሊሆን ይችላል። አንዳንድ ሰው ጸሎቱ እንዳለቀ ስብከት ላይ መድረስ ይፈልጋል ። ሁሉም ግን ለእግዚአብሔር ክብር ፣ ለሰው ጥቅም የሚደረግ አገልግሎት ነው ።

ቀጠሮን በሚመለከት ራሳችንን የረገምን ሕዝቦች ነን ። “የሀበሻ ቀጠሮ” እንላለን ። የሚገርመው ያረፈደው ሰውዬ ሳይቀር “ያው የሀበሻ ቀጠሮ አይደል” ይላል ። ቀጠሮ የሰውነት እንጂ የሀበሻና የፈረንጅ መለኪያ አይደለም ። ወላጆቻችን ቀጠሮ በጣም ያከብሩ ነበር ። ጠዋት ቀጠሮ ካላቸው እንቅልፍ አይተኙም ነበር ። ባለፈው ዘመን ከሰዓቱ በፊት የሚደርስ ትውልድ ነበረ ፣ በመካከሉ አርፍዶ የሚደርስ ትውልድ ተፈጠረ ። አሁን ደግሞ አርፍዶ የሚቀር ትውልድ እየመጣ ነው ። የሚገርመው የቀጠርነው ሰው ሲቀር እንደ መገላገል እየቆጠርን መምጣታችን ነው ። በአሁን ዘመን ቅሬታም እያለቀ ነው ። ቀጠሮ ለራስና ለሰው ያለን ክብር መግለጫ ነው ።

ቀጠሮን ለማክበር መርሳትንም ለማሸነፍ የሚረዱን ነገሮች፦

የማንችል ከሆነ ቀጠሮ መያዝ አይገባንም። ቀጠሮው ከተሰረዘም ቀደም ብለን ማሳወቅ ይገባናል ። ሰውን ቀጥሮ ስልክ ማጥፋት ነውር ነው ። ነጻ ፍጡር ነንና መገኘት ካልፈለግን ቀድመን ማሳወቅ ይገባናል ። በማስታወሻችን ላይ ቀጠሮአችንን ማስፈር ተገቢ ነው ። ማስታወሻውን በሚታይ ቦታ ላይ ማስቀመጥ መልካም ነው ። የመንገድን ሁኔታ ታሳቢ አድርገን ቀድመን መውጣት አስፈላጊ ነው ። የማይካስ የሰውን ጊዜ እንዳንበላ መጠንቀቅ ይገባናል ። ከቤተሰብ ጋር ከሆነ ወደ ቀጠሮ ቦታችን የምንሄደው ፣ ሕፃናት ሊያስረፍዱ ይችላሉና ቀድመን ማዘጋጀት አለብን ። ልጆች ካሉ ሴቶች ጫና ስለሚበዛባቸው “ቶሎ በይ” ከማለት ማገዝ የተሻለ ነው ። የሚገርመው ሙሽራ ማርፈድን እንደ ክብር የሚቆጥርበት አገር መሥርተናል ። እድምተኛ እየበላ ሙሽራን መጠበቅ የቅርብ ጊዜ ልማድ ነበር ። አሁን ግን አትብሉም ፣ ቶሎ አልመጣምም የሚል ሙሽራ አፍርተናል ። ይህ የትውልዱ መውደቅ ምልክት ነው ።

በቀጠሮአችን መሠረት ስንገናኝም የምንነጋገርበትን ርእስ መያዝ ከመጋጨትና ከመሰለቻቸት ይጠብቀናል። ስንገናኝ ጥሩና ሞቅ ያለ ሰላምታ መለዋወጥ ፣ ስናወራ ዓይን ለዓይን ተያይተን ማውራት ፣ የአክብሮትን ቃላት መጠቀም መልካም ነው ። ስንለያይ በስስት ለቀጣይ ግንኙነት በር በመክፈት መሆን ይገባዋል ። ቀጠሮ ማክበር የትልቅነት መለኪያ ነው ። ሰዎችን ስንቀጥር ከአቅም በላይ በሆነ ጉዳይ ሊቀሩ ይችላሉና መቀየም አይገባንም ። ሰዎችን ስንቀጥር የሚነበብ መጽሐፉ መያዝ ጥሩ ነው ። ቢያረፍዱ ደግሞም ቢቀሩ ጊዜውን መጠቀም እንችላለን ። ጊዜ ክቡር ነውና ቀጠሮ አክብሩ!

እግዚአብሔር ዘመናችሁን ይባርክ !

ይቀጥላል

ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
ሚያዝያ 15 ቀን 2016 ዓ.ም.
የሕይወት ሥነ ሥርዓት (15)

12- የመጣህበትን አትርሳ

ሕይወት መንገድ ነው ። መንገድ የመጣንበት ደግሞም የምንሄድበት ነው ። ሀብት ቢነጥፍ ፣ ጉልበት ቢከዳ ፣ ወዳጅ ጠላት ቢሆን ሕይወት ይቀጥላል ። ሁሉም ሰው የራሱ የሆነ ሕይወት አለው ። በእግዚአብሔር ፈቃድ የጀመረች ሕይወቱ በእርሱ ፈቃድ ትቆማለች ። ከበሽታ የተነሣ ቢመረር ፣ ከማጣት የተነሣ ቢያለቅስ ፣ ከወዳጅ ሞት የተነሣ ቢከፋው ሕይወት ትቀጥላለች ። አቀባበሉ ግን ቀጣዩን ብርሃን ወይም ጨለማ ያደርገዋል ። በአንድ ዓይነት መከራ ውስጥ የሚያልፉ ሁለት ሰዎች አንዱ ቢስቅ ሌላው ቢያለቅስ ጉዳዩ የአቀባበል ነው ። አቀባበሉ ያቀለዋል አሊያም ያከብደዋል ። ያመንነውን እንወርሳለንና “ይህ ክፉ ነገር ለበጎ ነው የመጣው” ስንል በጎ ይሆናል ። አቀባበል ጨለማውን ብርሃን ያደርጋል ። መንገድ ከፍታም ዝቅታም አለው ። ሕይወት መንገድ ናትና የክብር ዘመን እንዳለ ሁሉ የውርደት ዘመንም አለ ። አልጫ አልጫ የሚል ቃል ተናግረን እንደ ጥቅስ የሚነገርበት ዘመን አለ ። የጥበብ ቃል ተናግረን “ምነው ሞቶ ባረፈው” የምንባልበት ዘመን አለ ። አንዳንድ ሁኔታዎች መታገል ሳይሆን መታደል የሚያመጣቸው ሊሆኑ ይችላሉ ።

ተራራ የወጣው መንገደኛ ቁልቁለት እንደሚወርድ እርግጠኛ ነው ። ከተራራ ቀጥሎ ተራራ አይመጣምና ። የከበረም መዋረዱ አይቀርም ። “ፖለቲከኛና አትሌት በቃህ ካልተባሉ አያቆሙም” ይባላል ። እንደ ከበሩ ዞር ማለት ትልቅ ጥበብ ነው ። ከሐር መነሳንስ ወደ ጭቃ ጅራፍ ሳይለወጥ ዞር ማለት አዋቂነት ነው ። ይልቁንም በአገራችን ወረት በዙፋን ተቀምጦ እየገዛን ይመስላል ። “አንቱ” ያልነውን ሰውዬ “አንተ” ለማለት እንቸኩላለን ። መንገድ ተመዝማዛ ነው ። ቀጣዩ አልታይ እያለን የምንጨነቅበት ፣ ተስፋ ዘይቱ እንዳለቀ መቅረዝ ጭል ፣ ጭል የሚልበት ጊዜ ጥቂት አይደለም ። ተስፋ መቍረጥም የሕይወት አንድ አካል ነው ። ያልገባን ነገር ቢኖርም “እግዚአብሔር አዋቂ ነው” ማለት ያሳርፋል ። “እግዚአብሔር አዋቂ ነው” ማለት “እግዚአብሔር ያውቅልኛል” ማለት ነው ። መንገድ ሸካራ ነው ። ውስጣችን በሰዎች ክፋት የሚበከልበት ፣ ጥርጣሬ ቀናችንን የሚዋጋበት ጊዜ ብዙ ነው ። ሰዎችን ይቅር ለማለት ከራሳችን ጋር ግብ ግብ ውስጥ የምንገባበት ፣ ቂመኝነትን ዳግም ላለመጎዳት የሚጋረድ ጋሻ አድርገን የምንመለከትበት ጊዜ አያሌ ነው ። “ተበድዬስ ይቅር አልልም” እያልን እንዘፍናለን ። ይቅር የምንለውማ ስንበደል ነው ። ፍቅር የመበደል አጥር ሲሻገር እውነተኛ ይሆናል ።

ሕይወት መንገድ ነው ። መንገድ መነሻ አለው ፣ መንገድ መድረሻ አለው ። እግዚአብሔርን ማመን ያስፈለገን መነሻና መድረሻ ያለው ሕይወት ለመያዝ ነው ። እግዚአብሔርን ካላመንን ሕይወታችን መነሻና መድረሻ የሌላት ፣ መሐል ባሕር ላይ ያለ መቅዘፊያ የተለቀቀች ጀልባ ትሆናለች ። የመጣንበት የምንሄድበትን ይወስነዋል ። የመጣንበትን በትክክል ማሰብ ከቻልን ምስጋና በአፋችን ይሞላል ። ሰውን መበደል እንጸየፋለን ። ሌሎችን ለመርዳት እንነሣሣለን ። መካሪ ሁነን አዲስ ትውልድን እናበረታታለን ። ግፍን እንጸየፋለን ። ማንንም አንንቅም ። አዎ ሕፃናት ነበርን ። ሕፃናትን መውደድና ማክበር አለብን ። አዎ ዕራቁታችንን ተወልደናል ። ስለዚህ ድሀ ነበርኩ ማለት የሚያሳፍር አይደለም ። ያለ ፍትሕ ታስረናል ። ስለዚህ ያለ ፍትሕ ሌሎችን መጉዳት አይገባንም ። አንድ ድቃቂ ሣንቲም ሊቸግር እንደሚችል ኑሮአችን ምስክር ነው ። የመጣንበትን ብናስብ እጆቻችን ለመርዳት ይዘረጉ ነበር ።

አዎ የመጣህበትን አትርሳ ። የመጣኸው ካፈር ነው ። አንድ ቀን ወደ አፈር ትመለሳለህና ኩራትን ተው ። ፊደል ለማወቅ ብዙ ወራት የፈጀብህ ፣ በብዙ ጥረት አዋቂ የሆንህ ፣ የብዙዎችን ጉልበት የጨረስህ ነህና ሰውን “ደንቆሮ” ብለህ ለመሳደብ አትድፈር ። ዕድሉን ቢያገኝ ሁሉም ሊቅ ይሆን ነበር ። ያደግህበት ሰፈር ዛሬ ካየሃቸው ውብ ከተሞች የሚበልጥ ትዝታ ያለው ነውና ያደግክበትን ቀዬ ዞር ብለህ ተመልከት ። ያሳደጉህ እናቶች ፣ ዛሬም ረሀብ ዘመድ ሆኖ አልላቀቅ ያላቸው የአባትህና የእናትህ ጓደኞች አሉና ሄደህ ጠይቃቸው ፣ ካለህ ላይ አካፍላቸው ። ትንሹ ማሙሽ አድገህ ለመስጠት በመብቃትህ ፈጣሪያቸውን ባንተ ምክንያት ያመስግኑት ። መምህራኖችህ ዛሬ ከእነርሱ የበለጠ እውቀት ብትይዝም የወጣህባቸው መሰላል ናቸውና አክብራቸው ። ዋጋቸውንም ሂደህ ንገራቸው ። የወጣህበት መሰላል ለመውረድም ይረዳልና ወጣሁ ብለህ ገፍተህ አትጣለው ። አንተን አንቱ ያሰኘህ ሕዝብ ነውና ሕዝብህን አትናቅ ። ሕዝብ ያንተ ሎሌ ሳይሆን አንተ የሕዝብ አሽከር መሆንህን እመን ። የሥልጣን በትር አንድ ቀን ከእጅ ያመልጣል ። የደጁን ስትገፋ ልጅህ እንደ አቤሴሎም ለሞት ይፈልግሃል ። ሥልጣን ፀሐይ ነው ። ምንም ቢደምቅ መጥለቁ አይቀርም ። አዎ የድሀ ልጅ ነበርህና የመጣህበትን አትርሳ ። በማጣት ዘመንህ ፣ በእስር ወራትህ የገባኸውን ቃል ኪዳን አትዘንጋ ። ዛሬ ሽቱ ስለተቀባህ ሰው ሁሉ የሚሸት መስሎህ አትጸየፈው ። የአንድ ቀን ውኃ ስታጣ አንተም ለመበላሸት ቅርብ ነህ ። የመጣህበትን አትርሳ ። ይህችን ከተማ ስትቀላቀል የነበረህን መደናገር አትዘንጋ ። ስለዚህ ማንንም መጤ ብለህ አትናገር ። ሁሉም ሰው መጤ ነው ። አንድ ቀን ይሄዳል ። በዚህ ዓለም ላይ መሰንበት እንጂ መቅረት የለም ።

የመጣህበትን አትርሳ ። እግዚአብሔር ብቻውን አስተማረኝ ብለህ ያስተማሩህን አትካድ ። እግዚአብሔር ብቻውን ረዳኝ በሚል ዘይቤ የሰውን ውለታ አታጥፋ ። የእናቴን ጡት አልጠባሁም ፣ የማንም ውለታ አላለፈብኝም ብለህ አትገበዝ ። ያልተቀበልከው ምንም ነገር የለም ። ከተቀበልህም የምትመካበት አንዳች ነገር የለህም (1ቆሮ. 4 ፡ 7) ። የዛሬ ስኬትህ የሁልጊዜ ስኬት አይደለምና እንዳረጀ ወዳጅ በበላህበት ቤት ጓሮ አትለፍ ። እንደ ጎርፍ በመንገድ ያገኘኸውን ተሸክመህ አትጓዝ ። አንገት የተሠራው ለጌጥ ሳይሆን ዞሮ ለማየት ነው ። ከስንት ሞት አምልጠህ ፣ የወዳጅህን ሞት አትመኝ ። ካልጨመሩበት ይቀንሳልና ወዳጅህን ወዳጅ አገኘሁ ብለህ አትግፋው ። ወረት የሰይጣን ልጅ ያደርጋል ። እወድሃለሁ ያለህ ሁሉ አይወድህምና ወላጆችህን አትግፋ ። “የወረት ውሻ ስሟ ወለተ ጴጥሮስ ነው” ይባላል ። እፍ ለማንደድ ፣ እፍ ለማጥፋት ነውና ዛሬ ካገኘኸው ጋር እፍ አትበል ። የፊት ወዳጅህን ጨርሰህ ክፉ ነው አትበል ፣ የኋላው ይታዘብሃል ። አዎ የመጣህበትን ታውቀዋለህ የመጣህበትን አትርሳ ። የመጣህበት ሲጠፋህ የምትሄድበት ይጠፋሃል ። ወዳጅ በብር አይለወጥም ፣ ወዳጅ ውድ ነው ፣ በወርቅ አይለወጥም !

ከወዳጅህ ጋር ለማርጀት ያብቃህ !

ይቀጥላል

ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
ሚያዝያ 17 ቀን 2016 ዓ.ም.
የማርቆስ ወንጌል ትርጓሜ 16

ማር. 3: 6-12

ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
Audio
የማርቆስ ወንጌል ትርጓሜ 16

ማር.3፥ 6-12

ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
HTML Embed Code:
2024/04/27 01:39:53
Back to Top